ሥርዐተ ተክሊል ምን ማለት ነው?
ለተክሊል ጋብቻ መሟላት ያለባቸዉ ዋና ዋና መስፈርቶች ምንድን ናቸው ?
ዕድሜ
የሚጋቡት ወጣቶች ዕድሜአቸው ትዳር የሚጠብቀውን ሓላፊነት ለመወጣት ብቁ ሊሆኑ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህም አስቀድሞ በፍትሐ ነገሥት እንደተገለጠው ሴቷ 15 ወንዱ ደግሞ 18 ዓመት የሞላቸው መሆን አለባቸው፡፡ እንደዚህም ሆኖ ሌሎች ነገሮች ካልተሟሉ ከዚህ በላይ ቢሆን መልካም ነው፡፡
የአእምሮም ሆነ የአካላዊ ብቃት፡-
የሚጋቡት ወጣቶች በአእምሮም ጤነኛ ቢሆኑ አካላቸውም ከጋብቻ በኋላ ለሚፈጸመው የግብረ ሥጋ ግንኙነት ወይም ከሥነ ልቡናዊ ችግር የተነሣ የግብረ ሥጋ ግንኙነት መፈጸም ባይችል የቀረውን ወገን ወደ ሌላ ኃጢአት ይገፋፋልና የግድ አካላዊ ብቃት ሊኖር ያስፈልጋል፡፡ የአእምሮ ሁኔታም በትዳር የሚጠበቅበት ሓላፊነት ወይም ቤተሰብ የማስተዳደር ብቃት ሊኖር ያስፈልጋል፡፡
የኢኮኖሚ አቅም፡
የሁለቱም ተጋቢዎች ወይም ከሁለት አንደኛው ወገን ራሱን የቻለ ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ የኢኮኖሚ ዐቅማቸው ቤተሰቡን ለማስተዳደር በቂ መሆኑ ሊረጋገጥም ይገባል፡፡ በርግጥ ይህ ሁልጊዜ ላይሆን ይችላል፤ ፍቅር ካላቸው ሁለቱም ሠርተው ሊያፈሩ ይችላሉና፡፡
ስለ ትዳር ማወቅ
ተጋቢዎች ከመጋባታቸው በፊት ስለ ትዳር በአጠቃላይም ስለተክሊል ጋብቻ በሚገባ ሊያውቁ ያስፈልጋል፡፡ ትዳር በሌላ በሦስተኛ ሰው ግፊት የሚፈጸም ወይም ሌላው ስላደረገው ብቻ እስቲ ልሞክረው ተብሎ የሚገባበት ሕይወት አይደለም፡፡ ስለዚህ ከገቡበት በኋላ እንዳይቸገሩ ወጣቶች የትዳርን ምንነት አስቀድመው ሊያውቁ ያስፈልጋል፡፡ በተጨማሪም ስለ ሥርዐተ ተክሊል አስቀድመው በንስሐ አባታቸው ወይም ሰንበት ት/ቤታቸው ሊማሩ ይገባል፡፡
የንስሐ አባት ምስክርነት
እንግዲህ ተጋቢዎች እነዚህን ከላይ የተጠቀሱትን ነጥቦች ካሟሉ የተቀደሰው የሥርዐተ ተክሊል ጋብቻ ሊፈጸምላቸው ይቻላል፡፡ በተረፈ ሥርዐተ ተክሊል ከአጽዋማት ቀናት በስተ ቀር በማንኛውም ቀን ሊፈጸም ይችላል፡፡ ሥርዐተ ተክሊልን ለመፈጸም ወሳኙ ነገር የቀናቱ መለያየት ሳይሆን የተጋቢዎቹ ማንነት ነው፡፡
‹‹ መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር ነው፡፡ ለመኝታውም ርኩሰት የለውም ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል፡፡ ›› ዕብ ም፥፲፫ ቑ፥፬
ምንጭ : አባቶችህን ጠይቅ ይነግሩህማል
